ስርዓት አልባ የሆኑ ስርዓት አስከባሪዎቻችንን ማን ስርዓት ያስይዝልን??

Artist Azeb Worku

ቦታው ኤየርፖርት ፓርኪንግ (የሐገር ውስጥ በረራ)
ጊዜው ጠዋት 4 ሰዓት አካባቢ
እኔ እና ወንድሜ በጠዋት እንግዳ ለመቀበል ኤየርፖርት ተገኝተናል ከብዙ ሠዓታት ጥበቃ በኋላ እንግዳችን መጣችና ተቀብለናት ከፓርኪንግ ስንወጣ
አንድ መሳሪያ የታጠቀ ፌደራል ፖሊስ – ( በሐይለኛ ቁጣ እየደነፋ) አቁሙ
መኪናችንን አቆምን
ፌደራሉ – (በማመነጨቅ ) መንጃ ፈቃድህን አምጣ
ወንድሜ – ምን አጠፋሁ?
ፌደራሉ – ደርበህ ነው የቆምከው
ወንድሜ እረ እኔ በጭራሽ ከፓርኪንግ ነው የምወጣው
ፌደራሉ – አትለፍልፍ መንጃ ፈቃድህን አምጣ
ወንድሜ ሰጠው
ፌደራሉ – በል ሂድ ከዚህ
ወንድሜ – መንጃ ፍቃዴስ?
ፌደራሉ -( ደሜን አታፍላው በሚል ስሜቴ ) አንተ ሰውዬ አታነግረኝ ሂድ ብዬሃለሁ ሂድ መንገድ አትዝጋ
እኔ – (መስኮት ከፍቼ )መንጃ ፍቃዱስ?
ፌደራሉ – ምን አባሽ አገባሽ አንቺ? አንቺ ደግሞ ምን ቤት ነሽ? …………. ( ይሄ በነጥብ በነጥብ ያለፍኩት አጸያፊ ስድቡን ነው)
እኔ,- ( በንዴት )ለምን ትሰድበኛለህ ?
ፌደራሉ – ምን ታመጫለሽ ሂጅ ጥፊ ከዚህ
ፌደራሉ – መንጃ ፍቃዱን ይዞት ሄደ
አጠገቡ የነበረ አንድ ሰው ሊያግባባን ሞከረ፡፡ ስድባችንን ውጠን ትንሽ አስጨብጠን መንጃ ፍቃዳችንን ተቀብለን እንድንሄድ መከረን፡፡ አናደርገውም ትራፊክ ይዘን እንመጣለን አልን ቦሌ አደባባዩ ጋር ላገኘነው ትራፊክ ፖሊስ ሰላምታ ሰጥተን ጉዳያችንን አስረዳን ትራፊኩን ጭነን ወደ ኤየርፖርት ተመለስን ፡፡
ትራፊኩ ፌዴራሉ ን ጠየቀ
ፌደራሉ – በሚኒባስ የተከለከለ ቦታ አቁሞ ሰው ጭኖ ሲወጣ ነበር ብሎ ለትራፊክ ፖሊሱ ተናገረ
ወንድሜ – ይሄ ታክሲ አይደለም የድርጅት መኪና ነው ይቹ እህቴ ናት አለ
እኔም – ተሳፋሪ አለመሆናችንን ለማረጋገጥ ከሆነ የኔን መታወቂያ እና የሱን መታወቂያ አመሳክር አልን
ፌደራሉ – ትራፊክ ይዘሽ የመጣሽው ትራፊክ የምፈራ መሰለሽ
ሰዎቹ – በሰላም መፍታት ስትችሉ አከረራችሁት
ፌደራሉ – (እየደነፋ እና ትራፊክ ፖሊሱ ላይ እያፈጠጠ) ቅጣው
ትራፊክ ፖሊስ – በምን ልቅጣው
ትንሽ በዕድሜ ጠና ያለ ፌደራል ከወጣቱ ፌደራል አጠገብ ቆሞ – ደርቦ በመቆም ብለህ ቅጣው (ይሄን ያለው ጠና ያለው ፌደራል በሰዓቱ በቦታውም አልነበረም)
እኔ -እኔን ያለ አግባብ ሰድበኸኛል ይቅርታ እንድትጠይቀኝ እፈልጋለሁ
ፌደራል – (በተደፈርኩ ስሜት እየደነፋ) ምን ?
እኔ – አንተ ስርዓቱን ልታስከብር ቆመህ ስርዓት በሌለው መንገድ አጸያፊ ስድብ ሰድበኸኛል
ፌደራል- (በትዕቢት) እና ምን ታመጫለሽ ?
እኔ – እሺ ስምህን ነገረኝ
ፌደራል – አልነግርም
እኔ- ስምህን መጠየቅ መብቴ ነው አንተም መንገር ግዴታህ ነው
ፌደራል – ( በማመናጨቅ )ስሙን አልነግርም አለኝ ብለሽ ክሰሺ
ሌላ ፌደራል ፍለጋ ሄድኩ ኤየርፖርት መግቢያ በር ላይ መገናኛ ሬድዮ የያዘ ፌደራል አገኘሁ፡፡
ፌደራሉ – ( ጉዳዩን አዳምጦ ) ሊሰድብሽ መብት የለውም፡፡ ስሙን መንገርም ግዴታው ነው ተመልሰሽ እራሱኑ ጠይቂው እኔን እዚህ ነገር ውስጥ አትክተቺኝ…..
ተመለስኩ ወደ ፌደራሉ
ፌደራሉ በታላቅ ትዕቢት ከሌላ ፌደራል ጋር ቆሞ ይመለከተኛል
እኔ – ቀረብ አልኩትና የኔ ወንድም የስራ ባልደረባህን አነጋግሬው ነበር ስምህን መንገር ግዴታህ እንደሆነ ነግሮኛል፡፡
አጠገቡ የቆመው በዕድሜ ጠና ያለው ፌደራል- ስሙን ቢነግርሽ ምን ልታደርጊ ነው ?
እኔ – ሰላማዊ ሰውን ያለአግባብ ስለሚሰድብ እና ስለሚያወርድ ልከሰው
ጠና ያለው ፌደራል – በቃ አልናገርም አለሽ እኮ (በመሳለቅ) ከፈለግሽ የኔን ስም ያዢ ኢንስፔክተር መልካሙ ጥሎኝ ሄደ …
እደነዚህ ዓይነት ስርዓቱን ሊጠብቁ እና ስርዓት እና ሕግ ሊያስከብሩ የሚቆሙ ለሕግ የማይገዙ ስርዓት አልባ ፖሊሶች ሕብረተሰቡን ሲሰድቡ ሲያዋርዱ እና ሲሰድቡ ሊያስጠብቁት የቆሙለትን ሰርዓት ማሰደባቸውን እና ማስወቀሳቸውን ልብ ይሉታል? መንግስትስ አታሰድቡኝ ግዴታችሁን ተወጡ የሰዉን መብት አክብሩ ማለት የለበትም? ሲያሰድቡት በዝምታ ይመለከታል?

Leave a comment